የኢትዮጵያ ብሎጎች ምን ጻፉ ከሚያዚያ 21 እስከ 29

የእስክድር ነጋን መሸለም ፡ የርእዮት አለሙን ለሽልማት መታጨት ይህንን ተከትሎ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው የፕሬስ ሁኔታ የተሰጡ አስተያየቶች በዚህ ሳምንት የኢትዮጵያ ብሎጎች የትኩረት ነጥቦች ነበሩ:: እስክንድር ሽልማቱ ይገባዋል የርእዮት አለሙም ለሽልማት መታጨት አስደስቶናል የሚሉ በርካታ ጽሁፎች ተነበዋል:: ጥቂቶቹን ላቃምሳችሁ:፡ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም ስለ እስክንድር አንድ ጽሁፍ አሰነብበዋል:: አንድ አንቀጽ እንካችሁ፦

በተረትና በባህላዊ ወጎች በርካታ የተለያዩ ጀግኖች አሉ፡፡አንዳንዶች በሚያጋጥማቸው አደጋ ወቅት በሚያሳዩት የሞራል ጥናካሬ ይጀግናሉ፤አንዳንዶች ደሞ ለክብራቸውን ለዓላማቸውበመቆማቸው ይጀግናሉ፡፡ እንዲሁም አንዳንዶች ጠላቶቻቸውን በፍልሚያው ሜዳ በመግደላቸው ድል በማሸነፋቸው ጀግና ይባላሉ፤ለፍቅር የተሰዉ ጀግኖችም አሉ፤ዘመናዊና ባህላዊ ጀግኖችም ይታያሉ፤ያልታወቀላቸውም ጀግኖች አሉ፤ደግሞም የድል አጥቢያ ጀግኖችም አሉ፡፡ በዚህም ሆነ በዚያ ሁሉም የሚጋሩት አንድ ባህሪ አላቸው፡፡መስዋእትነት፤ታማኝነት፤ጥንካሬ፤ቆራጥነት፤ እርግጠኛነት፤ ያለማወላወል እና ሌሎችም ሁኔታዎች፡፡
ከዚህ ሁሉ በተለየ አካሆን ግን እስክንድር ጀግና ነው! እስክንድር እውነትንና ሃሳቦችን ብቻ በመያዝ የሚዋጋ ጀግና ነው፡፡መነሻው ሃሳብ መድረሻው ሃቅ ነው፡፡ መቀላመድን በእውነት ሰይፍ ያነበረክካል፡፡መሰረተ ቢስና መደለያ ማታለያ የሆኑ ሀሳቦችን በሚቻል፤በሚታመን፤ትክክለኛና ሕዝባዊ በሆነ ሃሳብ ይረታዋል፡፡ብእር ብቻ የጨበጠው እስክንድር ነጋ የሚዋጋው በብእሩ ነው፡፡

ሙሉውን ጽሁፍ ይህችን ጠቅ በማድረግ ያንብቡት:: ስለ ርእዮት ከተጻፉት ደግሞ የአቤ ቶኪቻውን ያዙልኝ አቤ ዜናውም ትንተናውም እንግዲህ በጫወታ መልክ ነው::ከሱም አንድ አንቀጽ ላካፍላችሁ::

በፍትህ ጋዜጣ አምደኛ ሆና በምትሰራበት ወቅት “አሸበርሽ” ተብላ የታሰረችው ርዮት አለሙ “ኢንተርናሽናል ውመን ሚዲያ ፋውንዴሽን” የተባለ ድርጅት የሚዲያ ጀግና ሲል ለሽልማት መረጣት።ሽልማቱ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ራስን ለአደጋ አጋልጦ በጋዜጠኝነታቸው ለተጉ ሴቶች የሚሰጥ ሲሆን፤ ከርዮት አለሙ ጋር አንዲት የፓልስቲን እና አንዲት የአዠርባዣን ጋዜጠኞች ለሽልማቱ ተመርጠዋል።

የአቤ ብሎግ ቢታገድም ብዙ ሀገር ውስጥ የሚታተሙ መጽሄቶች ጽሁፎቹን ያትሟቸዋል:: አቤ ሌላም አንድ ትኩረቴን የሳበ ጽሁፍ አስነብቧል:: ስለሳንሱር ከመጀመሪያው አንቀጽ፦

እኔ የምለው ወዳጄ ሳሱር ነብሴ ድጋሚ መጣች አይደል እንዴ!? እሰይ! እልል በሉ እንጂ። ድግስ አትደግሱም እንዴ!? ጠላው ይጠመቅ፣ ድፎው ይደፋ፣ ቡናውም ይፈላ፣ ፈንዲሻው ይፈንደሽ፣ እጣን ሰንደሉ ተጫጭሶ ቄጤማውም ይጎዝጎዝ። በዓሉ የትንሳኤ በዓል ነውና ሁሉም ሰው ይደሰት።

አቤ ባሽሙር ተደሰቱ ቢለንም ይሄ እንግዲህ ብሎጎችን ከማገድ ያልተናነሰ ህግን የሚጥስ ነው:: የሀገሪቱ የአየር ሞገድ በአንድ እይነት ድምጽ ብቻ መሞላቱ በርግጥ አሳሳቢ ችግር ነው:: ወደ ተስፋዬ አለማየሁ አለፍኩ በሁለት ሃገራት ያሉ የሚመስሉ የመገናኛ ብዙሃን− የግል እና መንግስት ጋዜጠኝነት ሲፈትሽ በሚል ርእስ ኢትዮጵያ ውስጥ ልማታዊ ጋዜጠኝነት አለ ብለው ለሚከራከሩ ወገኖች መልስ የሚሆን በግል እና በመንግስት የመገናኛ ብዙሃን ላይ ታትመው የወጡ ዜናዎችን በመሰብሰብ አጠር ያለ ይዘታዊ ትንተና ሰርቶ ግንዛቤ የሚያስጨብት ጽሁፍ አስነብቧል:: እንደ ማጓጓያ አንድ አንቀጽ ላቅርብ:

እስቲ ጥቂት ስለ ጋዜጠኝነት አላባውያን እናውጋ እና ከዚያ ወደ ተነሳሁበት ሃሳብ አንድ ሁለት እያልን አብረን እንዘልቃለን፡፡ ከጋዜጠኝነት አላባዎች ቀዳሚዎቹ እና ዋነኞቹ ነፃ ትክክለኛ እና ሚዛናዊ መረጃን ለህዝብ ማድረስ ናቸው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ለህዝብ ታማኝ በመሆን ለእውነት ዘብ መቆም ከአንድ ጋዜጠኛ ከሚጠበቁበት መሰረታዊ ግዴታዎች ውስጥ ዋነኞቹ ናቸው፡፡ ለእውነት ዘብ መቆም እና ለህዝበ ታማኝ መሆን፡፡ እነዚህ ሁለት ነጥቦች በዋነኛነት ላተኩር የፈልግኩባቸው ነጥቦቼ እንጂ ሌሎቹን ዘንግቼ አይደለም፡፡ ለእውነት ዘብ መቆምን እና ለህዝብ መታመንን ይዘን አብረን እንዘልቃለን፡፡ እነዚህን ሁለት ነገሮችን በዋነኛነት ያልቋጠረ ጋዜጠኛ ለሌሎቹ ግድ ላይኖረው ይችላል፡፡ ሁለቱን በመሰረታዊነቱ ከያዝን በኋላ ግን ልማትን ጨምረን በሃገራችን ያለውን የጋዜጠኝነት ትግበራ እንፈትሸዋለን፡፡ ልማት ስንጨምርበት ደግሞ ለአንድ ማህበረሰብ የጋዜጠኝነት እና የጋዜጠኛው ሃላፊነት እና አስፈላጊነት በጣም ከፍ ይላል፡፡ ሃላፊነትን የሚሸከም ደንደን ያለ ትከሻ እና ብርቱ ጉልበት ይልጋል፡፡ ጋዜጠኝነት ከባድ ሃላፊነት ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ልማታዊ ጋዜጠኝነት፡፡

ሙሉውን ጽሁፍ ለማንበብ እዚህ ላይ ጠቅ ያድርጉ::

ከተስፋዬ የመገናኛ ብዙሃን የዘገባ ሽፋን ይዘታዊ ትንተና ጋር በቀጥታ ግንኙነት ስላለው ርዕሰ ጉዳይ ልለፍ:፡ ላለፉት አስራ አንድ እና አስራ ሁለት ሳምንታት በኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እና በእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ወይም መጅሊስ መካከል የነበረው አለመግባባት እየተካረረ በመምጣቱ መንግሥት ሐሙስ ዕለት ባወጣው መግለጫ ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ ሁከት ለመፍጠር እየሞከሩ ናቸው ለሚላቸው ወገኖች ሕገመንግሥታዊ ሥርዓቱን እንዲያከብሩ ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል :: መግለጫው እስከሚሰጥበት እለት ድረስ ቀን የመንግስት የመገናኛ ብዙሃን ስለተፈጠረው አለመግባባት እና በአወልያ ትምህርት ቤት እና በታላቁ አንዋር መስጊድ ዘውትር አርብ ለሶስት ወራት ገደማ ሲካሄድ ስለነበረው የተቃውሞ መግለጫ ብዙም አልዘገቡም ነበር:: መግለጫውን ተከትሎ ብሎጎች እና የማህበራዊ ድረገጽ ተጠቃሚዎች ግን የትኩረት ነጥባቸው አርገውት ነበር:: ኢትዮ አንድነት የተሰኝ ብሎግ ይህንን ጉዳይ በማስመልከት ሁለት የሌሎች ሚዲያ ዘገቦችን አስነብቧል። እዚህ እና እዚህ ላይ ጠቅ ቢያደርጉ ያገኟዋቸዋል::

አቤል በዚህ ሳምንት በቅርቡ 82ኛ የልደት በአላቸውን ስላከበሩት ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም አስነብቦናል:: ኢትዮጵያዊው ጆርጅ ኦርዌል ይላቸዋል:: እስቲ አንድ አንቀጽ፦

መቼም ‘Animal farm’ን የሚተካከል ተሳልቆ (ሳታየር) አላነበብንም፡፡የዚህ መጽሐፍ ደራሲ የብዕር ስሙ ጆርጅ ኦርዌል ሲሆን ትክክለኛ ስሙ ኤሪክ ብሌር ይሰኛል፡፡ዛሬ ስሙን ላነሳሳው የፈለኩት ያን ጋዜጠኛ፣ መምህር ፣ ወታደር እና የተባ ብዕረኛ ሳይሆን ኢትየጵያዊውን ጆርጅ ኦርዌል ነው ፡፡ ይህ ኢትዮጵያዊ መምህር ፣የካርታ እና ጂኦግራፊ ባለሙያ ፣ የዕድሜ ልክ ሐያሲ ፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ፣ በምክንያት ፓለቲከኛ ሲሆን የኛን እንስሳት ዓለም ለማሳየት እንደጆርጅ ኦርዌል ልብወለድ መጻፍ አላስፈለገውም፡፡ ለብዙ አመታት ስለ ሕገ አራዊትና ሕገ ሐልዮት በግልጽ እየተነተነ አሳየን እንጂ፡፡ ሰው እንድንሆን መሞገት ከጀመረ እንደሰነበተ የምንረዳው ከሁለት አገዛዞች በፊት በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት በተደረገ የዕድሮች ስብሰባ ያደረገውን ንግግር ስናነብ ነው፡፡

ሙሉውን ጽሁፍ ለማንበብ እዚህ ላይ ጠቅ ያድርጉ::

በነገራችሁ ላይ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም በስማቸው የተሰየሙ ብሎጎች አላቸው:: አንዱ ቆየት ያለ እና ፕሮፌሰር መስፍን ለተለያዮ መገናኛ ብዙሃን የሰጡትን ቃለምልልስ እና አንድ አንድ ስራዎቻቸውን የያዘ ነው እዚህ ላይ ጠቅ ቢያደርጉ ያገኙታል:: ሁለተኛው ውቅታዊ ጽሁፎችን የሚያስነብብ ብሎግ ነው:: በዚህ ሳምንት አንድ በፍትህ ጋዜጣ ላይ የታተመችን የመንግሥት ሌቦች አደራ-ቢስነትና ሕዝብ ኃላፊነት በሚል ርእስ የተጻፈች ጽሁፍ በድጋሜ አስነብበዋል:: ይችን ጠቅ በማድረግ ያንብቡት:: ፍትህ ጋዜጣን ለማታገኙ እስቲ አንድ አንቀጽ፦

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተደጋጋሚ ስለመንግሥት ሌቦች እየተናገረ ነው፤ ሌቦቹን ግን እሱም አያውቃቸው፤ እነሱም እየሰሙት አይደለም፤ የመንግስት ሌቦች የተባሉት የሚግጡባቸው ዋናዎቹ መስኮች ታክስ፣ መሬትና የንግድ ውድድር መሆናቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጾአል፤ ከዚህም በላይ የተባሉትን የሌብነት መስኮች ከለምነት ወደበረሃነት ለመለወጥ የኢትዮጵያ ህዝብ ኃላፊነት አለበት ያለ መሰለኝ፤ ሥልጣን ሳይኖር ኃላፊነት ከየት ይመጣል? እንግዲህ የፌዴራል ፖሊሱንና ሌላውን አልፎ፣ የደኅንነቱን ሰራዊት አልፎ፣ የጸረ-ሙስና ኮሚሽንን አልፎ፣ ዓቃቤ ሕግን አልፎ ሕዝብ እነዚያን ለምለም መስኮች ማድረቅ እንዴት ይችላል? ሌቦቹ ያሉት በመንግስት ጎራ ብቻ ሳይሆን በህዝብም ጎራ እንደሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቆም አድርጎአል፤ እንዲህ ከሆነ ‹‹አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ›› የሚባለው ሁኔታ ሰፍኖአል ማለት ይመስላል፤ ይህ እውነት ከሆነ ሌብነት ሥርዓት ሆኖአል ማለት ነው።

በፍቄ በዚህ ሳምንት ስለአብዮት አስነብቦናል:: አብዮት ምን እንደሆነ እና ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው ነባራዊ ሁናቴ ጋር በማዛመድ አንድ ብሏል:: አንድ አንቀጽ፦

አብዮት – ከዚህ ቀደም እንዳወራነው – የእንግሊዝኛውን Revolution እንዲተካ ‹‹በደርግ›› የተመረጠ፣ የግዕዙን ቃል ‹አበየ› (Revolut) መሠረት አድርጎ የተሰየመ ቃል ነው፡፡ አብዮት – መንግሰትን ወይም ርዕዮተ ዓለምን የመተካት ሒደት ነው፤ አብዮት – ድንገታዊ እና ፈጣን ክስተት ነው፡፡

ሙሉውን ጽሁፍ ለማንበብ ትይይዙ ላይ ጠቅ ቢያደርጉ ይከፍትሎታል::

በመጨረሻም አሁን አሁን ስነ:ጽሁፋዊ ብሎጎች እየተበራከቱ ናቸው:: ዛሬ አንድ ጀባ ልበላችሁ እና የብሎግ ክለሳዬን ላብቃ :: ቤዋዬ ይባላል የብሎጉ ስም ሙሉ በሙሉ ለስነጽሁፍ የተከፈተ ብሎግ ነው:: በዝህ ሳምንት አጭር ልቦለድ አሰነብቦናል:: መሳጭ ቋንቋው እና አዝናኝ አተራረኩ ደስ ይላል:: ሙሉውን ጽሁፍ ለማንበብ ትይይዙ ላይ ጠቅ ቢያደርጉ ይከፍትሎታል:: መልካም ሳምንት::

One thought on “የኢትዮጵያ ብሎጎች ምን ጻፉ ከሚያዚያ 21 እስከ 29

  1. ቤዋዬ ይባላል የብሎጉ ስም ሙሉ በሙሉ ለስነጽሁፍ የተከፈተ ብሎግ ነው?? where is the link Endlak?

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.